Sunday, March 22, 2015

የኢትዮጵያ ተዋጊ ጄቶች፤ የኤርትራን የወርቅ ማዕድን ማውጫ፤ ሚሻን በቦንብ ደበደቡ

ኢ.ኤም.ኤፍ) የኤርትራ ኢኮኖሚ ዋልታ እንደሆነ የሚነገርለት፣ በማይ እዳጋ የሚገኘው የሚሻዕ ወርቅ ማዕድን ካምፓኒ በአየር ተደብድቧል። ተያይዞ የደረሰን ዘገባ እንዳመለከተው ከሆነ፤ የአየር ጥቃቱን ያደረሰው በወያኔ የሚመራው ወታደራዊ ኃይል ሲሆን፤ በጥቃቱም የወርቅ ማውጫው ክፉኛ መጎዳቱን ለማወቅ ችለናል። ከአስመራ 65 ማይል ርቀት ላይ የሚገኘው የወርቅ ማዕድን በአየር መመታቱ ከተሰማ በኋላ፤ በተለይ የአስመራ ነዋሪ ስጋት ላይ ወድቋል። የሰሞኑ የአስመራ ነዋሪዎችም መነጋገሪያ፤ “በመጀመሪያ ደረጃ የአየር ክልላችን ሲጣስ በራዳር ታይቶ፤ በጄቶቹ ላይ ቅጽበታዊ ምላሽ ለምን አልተሰጠም?” የሚል ጥያቄ አስነስቷል። ይህንንም ጥያቄ ተከትሎ “እኛስ ምን ዋስትና አለን?” የሚሉ ይገኙበታል።


ከአንድ ቀን በፊት በኤርትራ እንደሚንቀሳቀስ ይፋ ያደረገ ኃይል፤ በዚሁ የወርቅ ማዕድን ላይ ጥቃት ማድረሱን ገልጾ፤ በትግርኛ የተጻፈ ወረቀት በከተማው ማሰራጨቱ ይታወሳል። በዚህ በራሪ ወረቀት ላይ ጥቃቱን የፈጸሙት የኤርትራን አስተዳደር በመቃወም መሆኑን ገልጾ ነበር። የአሁኑም ጥቃት ይህንኑ ተከትሎ የተሰነዘረ ይመስላል።
በአሁኑ ሰአት በማዕድን ማውጫው ላይ የደረሰው አደጋ ለህዝብ ይፋ አልሆነም። ነገር ግን በቃጠሎው ምክንያት ከርቀት የሚታየው ጭስ በሚስጥር የተያዘውን ጥቃት እያሳበቀ ነው።
ኤርትራ ከዚህ የማዕድን ማውጫ በአመት እስከ 400 ሚሊዮን ዶላር ታገኛለች። የዚህ ማዕድን ስፍራ መመታት፤ የአገሪቱን የኢኮኖሚ ኃይል በእጅጉ ይጎዳዋል። በሌላ በኩል ደግሞ በወያኔ የሚመራው መንግስት ጠብ አጫሪነት እንደዚሁ አነጋጋሪ ሆኗል። ጥቃቱን የሚደግፉ እና የሚቃወሙ በሁለት የተለያዩ ጎራ ሆነው፤ የሃሳብ ፍጭት በማድረግ ላይ ናቸው። በዚህ ሁሉ መሃል ግን የሚሻዕ ወርቅ ማዕድን ማውጫ ግቢ አሁንም በእሳተየነደደ ነው።


No comments:

Post a Comment