Tuesday, June 17, 2014

በሃረር ከፍተኛ የውሃ እና የምግብ ዘይት ችግር ተከሰተ


ኢሳት ዜና :-ወኪላችን ከስፍራው እንደዘገበው በከተማዋ በተለይም ቀበሌ 14፣ 15፣ 16፣ 17፣ 18 እና 19 እንዲሁም በሸንኮራ፣ ጀጎልና ቀለዳምባ አካባቢዎች ከፍተኛ የውሃ እጥረት በመከሰቱ ህዝቡ የጀኔሪካን ውሃ በውድ ዋጋ ለመግዛት ተገዷል።
የክልሉ የውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ከአንድ አመት ከስድስት ወር በፊት ከሃረር በ75 ኪሜ ርቀት ላይ አሰሊሶ  በሚባለው ቦታ ከ80 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ካስቆፈራቸው 17 የውሃ ጉድጓዶች መካከል 6 ቱ በመደፈናቸው ችግር መፈጠሩ ታውቋል። በስራ ላይ ከሚገኙት 11 ጉድጓዶች መካከል 2ቱ ተመሳሳይ የመደፈን እጣ እየገጠማቸው ነው።
ጉድጓዶቹ ከመቆፈራቸው በፊት ባለሙያዎች አስቀድመው አስጠንቅቀው የነበረ ቢሆንም፣ በከተማው ውስጥ አጋጥሞ የነበረውን አሳሳቢ የውሃ ችግር ለመቅረፍ በሚል በፖለቲካ ውሳኔ ከፍተኛ ወጪ ወጥቶባቸው እንዲገነቡ ተደርጓል።
በሌላ ዜና ደግሞ መንግስት የሚያከፋፍለው ዘይት በከተማው ውስጥ በመጥፋቱ ፣ ቀድሞ 115 ብር ይሸጥ የነበረው ዘይት ነጋዴዎች 175 ብር እየሸጡ ሲሆን በአገር ውስጥ የሚመረተው ዘይት ደግሞ በሊትር 40 ብር እየተሸጠ ነው።
በከተማዋ የተከሰተውን የውሃ እና የዘይት እጥረት በተመለከ የመንግስት ባለስልጣናትን ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።

No comments:

Post a Comment