Tuesday, August 8, 2017

በኦሮምያና ሶማሊ ድንበር አካባቢ ያሉ ነዋሪዎች ተቃውሟቸውን እንደሚገፉበት ገለጹ

ኢሳት ዜና ( ነሃሴ 2 ቀን 2009 ዓም) በኦሮምያና ሶማሊ ድንበር አካባቢ ያሉ ነዋሪዎች ተቃውሟቸውን እንደሚገፉበት ገለጹ
በቅርቡ በኦሮምያና ሶማሊ ድንበር ከተማ በሆነው ጭናክሰን ከተማና አዋሳኝ ወረዳዎች የተካሄደው ተቃውሞ ሊቀጥል ይችላል በማለት ነዋሪዎች እያስጠነቀቁ ነው። ውጥረቱ አሁንም ድረስ መኖሩን ከስፍራው የደረሰን መረጃ አመልክቷል። ቀደም ብሎ የኦሮምያና የሶማሊ ክልል መሪዎች ባደረጉት ስምምነት መሰረት ድንበር የመከለሉ ስራ እየተሰራ ሲሆን፣ የውዝግቡ መነሻ የሆነው ጭናክሰን ውስጥ የሚገኘው 5 መንደሮች ያሉት አንድ ቀበሌ ነው። ቀበሌው ከዚህ ቀደም ተካሂዶ በነበረው ማካለል ውሳኔ ሳይሰጥበት በሁለቱም ክልሎች ሲተዳደር ቆይቷል። የኦሮምያ ክልል ቀደም ብሎ በሶማሊ ክልል የነበሩና በክልሉ ውስጥ እንደልብ ለመገናኘት ይጠቅሙኛል ያላቸውን 3 መንደሮች እንዲሰጡት፣ በመልሱ በኦሮምያ ክልል ያሉ 3
መንደሮችን ለሶማሊ ክልል ለመስጠት ስምምነት ላይ መደረሱን ተከትሎ፣ የአካባቢው ህዝብ “ እንዴት እኛ ሳናውቅና ሳንፈቅድ ወደ ሶማሊ ክልል ታካትቱናላችሁ” በማለት ተቃውሞ አንስቷል።
የክልሉን ፐሬዚዳንት ለማ መገርሳን እያወገዙ የሚገኙት እነዚህ ነዋሪዎች፣ በግዴታ ወደ ሌላ ክልል የምንገባ ከሆነ ከፍተኛ ግጭት ይነሳል በማለት አስጠንቅቀዋል። የኦሮምያ ክልል በጭናክሰንና ጃርሶ መካከል የሚገኘውን ቦታ ካልተረከበ፣ እንደልብ ለመዘዋወር እንደሚቸገርው በመግለጽ ፣ ቦታዎቹ እንዲሰጡት ጠይቆ ተፈቅዶለት ነበር። የሶማሊ ክልል በበኩሉ ተለዋጭ መሬት ካልተሰጠው በስተቀር ቦታዎችን ለኦሮምያ ክልል ማስረከብ አይፈልግም። በህዝቡ ተቃውሞ የተነሳ የድንበር ማካለሉ አጣብቂኝ ውስጥ መግባቱንም ነዋሪዎች ይገልጻሉ።

No comments:

Post a Comment