Thursday, August 3, 2017

የኦነግን አላማ ስታራምዱ ነበር የተባሉ 31 ተከሳሾች ተከላከሉ ተባሉ

የማርያም ፀበል እድርን በሽፋንነት በመጠቀም የኦነግ ወጣቶች ክንፍ የሆነውን ቄሮ ቢልሱማ በማደራጀት፣ አባላትን በመመልመል፣ የመሰብሰቢያ ቦታዎችን በመለየት እና በማዘጋጀት የኦነግን አላማ ስታራምዱ ነበር የተባሉ በእነ ሀብታሙ ሚልኬሳ የክስ መዝገብ የተከሰሱ 31 ግለሰቦች እንዲከላከሉ ብይን እንደተሰጠባቸው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በፌስቡክ አካውንቱ ላይ ዘግቧል፡፡ በመዝገቡ ላይ ሁለት ክሶች የቀረቡ ሲሆን 1ኛ ክስ በ1ኛ ተከሳሽ ሀብታሙ ሚልኬሳ እና 2ኛ ተከሳሽ ረዳት ሳጅን ጫላ ፈቃዱ ላይ የቀረበ ነው፡፡
ሁለቱ ተከሳሾች ‹‹የቄሮ ቢሉስማ ሊቀመንበር እና ምክትል ሊቀመንበር በመሆን አባላት የኦነግን ባንዲራ እንዲይዙ በማድረግ ለድርጅቱ ታማኝ እንዲሆኑ፣ በእውቀታቸው፣ በጉልበታቸውና በገንዘባቸው የድርጅቱን አላማ ማጠናከር እንዳለባቸው ቃል በማስገባት፣ ድርጅቱን ለማጠናከር አባላት መዋጮ እንዲያወጡ በማድረግ፣ ለገቢ ማሰባሰቢያ የመፅሃፍና የኦነግ ባንዲራ ሽያጭ እንዲያከናውኑ እና ሌሎች ትዕዛዞችንም በአመራርነት በማስተላለፍ›› ተሳትፈዋል የሚል ዝርዝር ክስ ቀርቦባቸዋል፡፡ 1ኛ እና 2ኛ ተከሳሽ በ1996 ዓ.ም የወጣውን የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ አንቀፅ 32 (1/ሀ) እና የፀረሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652 /2001 አንቀፅ ሁለት ስር የተደነገገውን በመተላለፍ በአመራርነት ወይንም በውሳኔ ሰጭነት ተላልፈዋል በሚል ተጠቅሶባቸው የነበረውን ክስ እንዲከላከሉ ተበይኖባቸዋል፡፡ ይህ አንቀፅ ከ20 አመት እስከ እድሜ ልክ እንደሚያስቀጣ በአዋጁ ላይ ተቀምጦአል፡፡
ሁለተኛ ክስ ከ3ኛ እስከ 32ኛ ባሉት ተከሳሾች ላይ የቀረበ ሲሆን ተከሰሾቹ ቀድሞ ተከሰውበት የነበረውን በ1996 ዓ.ም የወጣውን የወንጀለኛ መቅጫ አንቀጽ 32/1ሀ እና የፀረ ሽብርተኝነት አዋጁን ቁጥር 652/2001 አንቀፅ 7/1 ስር የተደነገገውን በመተላለፍ የቄሮ ቢሉሱማ አባል በመሆን፣ስብሰባዎች ላይ በመገኘት እና አባላትን በመመልመል በማንኛውም መንገድ በአባልነት ተሳትፋችኋል ተብለው የቀረበባቸውን ክስ እንዲከላከሉ ብይን ተሰጥቶባቸዋል፡፡ ከተከሳሾቹ መካከል 18ኛ ተከሳሽ ካሳሁን ሙሊሳ በህመም ምክንያት ሆስፒታል ስለገባና ፍርድ ቤት መምጣት ስላልቻለ ብይኑ በማረሚያ ቤት እንዲደርሰው ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል 22ኛ ተከሳሽ አብዲሳ ቦካ ቱጅባ በቃጠሎው ወቅት በመገደሉ ክሱ እንደተቋረጠ ተግለፆአል፡፡ የ26 አመት እድሜ የነበረው ወጣት አብዲሳ ደቡብ ክልል ውስጥ ሶዶ ከተማ በመምህርነት ሙያ ተሰማርቶ የነበር ሲሆን አዲስ አበባ በመጣበት ወቅት ተይዞ እንደታሰረ ተዘግቧል። ሟች አብዲሳ ቦካ ህዳር 9/2008 ዓ.ም በቦሌ ቡልቡላ ላይ ተካሂዷል ተብሎ በክሱ ላይ በተጠቀሰው ስብሰባ ላይ ተገኝቷል፣ የፕሮግራሙ የመክፈቻ ንግግር አድርጓል እና የድርጅቱ ገቢ ማስገኛ የሚሆን ገንዘብ አሰባስቧል የሚል ክስ ቀርቦበት እንደነበር የክስ መዝገቡ ያስረዳል፡፡
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ ሀምሌ 27/209 ዓ.ም ብይኑን ከሰጠ በኋላ 1ኛ እና 2ኛ ተከሳሽን ጨምሮ 20 ተከሳሾች የመከላከያ ምስክር እናቀርባለን በማለታቸው ከህዳር 11- 15 /2010 ዓ.ም መከላከያ ምስክሮቻቸውን እንዲያቀርቡ ቀጠሮ ተሰጥቷቸዋል፡፡ ቀሪዎቹ ተከሳሾች እንደማይከላከሉ በማሳወቃቸው ለፍርድ ነሃሴ 4/2009 ዓ.ም ተቀጥረዋል፡፡ ህዳር 19/2008 ዓ.ም ተይዘው ማዕከላዊ ታስረው ከነበሩት 58 ግለሰቦች መካከል 26ቱ ማዕከላዊ ታስረው ከቆዩ በኋላ ከእስር ተፈትተዋል፡፡


No comments:

Post a Comment