Tuesday, August 8, 2017

በዲያስፖራ ቀን በአል ላይ የተገኙ የዲያስፖራ አባላት መሬት ሳያገኙ ወደ መጡበት ተመለሱ

ኢሳት ዜና ( ነሃሴ 2 ቀን 2009 ዓም) በዲያስፖራ ቀን በአል ላይ የተገኙ የዲያስፖራ አባላት መሬት ሳያገኙ ወደ መጡበት ተመለሱ
በቅርቡ በሃረር ከተማ የተከበረውን የዲያስፖራ ቀን በማስመልከት የክልሉ ፕሬዚዳንትና የኢህአዴግ ጽ/ቤት በጋራ በመሆን፣ የ የዲያስፖራ አባላት በበአሉ ላይ የሚገኙ ከሆነ መሬት እንደሚሰጣቸው ቃል ተገብቶላቸው የነበረ ቢሆንም፣ የተገባላቸው ቃል ባለመከበሩ ዝግጅቱን አቋርጠው ወደ መጡበት በኪሳራ ተመልሰዋል፡፡ 

ምንጮች እንደገለጹት የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ ሙራድ አብዱላሂ ወደ ተለያዩ አገራት በመዘዋወር የዲያስፖራ አባላቱ በዝግጅቱ ላይ የሚገኙ ከሆነ መሬት እንደሚሰጡዋቸው ቃል ገብተውላቸው ነበር። የዲያስፖራ አባላቱም በበአሉ መክፈቻ ማግስት ፣ “ቃል የተገባልንን መሬት አሳዩን እንጅ” ብለው ሲጠይቁ፣ ፕሬዚዳንቱ “ በቅድሚያ በማህበር ተደራጅታችሁ ኑ” የሚል መልስ ሰጥተዋቸዋል። የዲያስፖራ አባላቱ በበኩላቸው፣ “ የመጣነው ከ አውስትራሊያ፣ አወሮፓ፣ አሜሪካና ካናዳ ነው፣ እርስ በርስ አንተዋወቅም። እንዴት ነው የማንተዋወቅ ሰዎች በማህበር ልንደራጅ የምንችለው፣ እንደራጅ ብንልስ እንዴት በአጭር ጊዜ ልንደራጅ እንችላለን፣ በፊት ስትጋብዙን በበአሉ ላይ እንድንገኝላችሁ አታላችሁን ነው” በማለት ዝግጀቱን አቋርጠው ብዙዎች ተመልሰዋል።
በአሉም ከመክፈቻው እለት ውጭ ከመቼውም ጊዜ በላይ ቀዝቅዞ የታየ ሲሆን፣ ሁኔታው በዚህ ከቀጠለ አጠቃላይ የዲያስፖራው ቀን በአል ፕሮግራም ሊሰረዝ ይችላል ተብሎአል።

No comments:

Post a Comment