Tuesday, October 25, 2016

አምነስቲ ኢንተርናሽናል የአሜሪካ ህግ አውጪ አካል በኢትዮጵያ መንግስት ላይ የውሳኔ ሃሳብ እንዲያጸድቅ አለም-አቀፍ ዘመቻ በማካሄድ ላይ መሆኑን ገለጸ

ኢሳት (ጥቅምት 15 ፥ 2009)
የአሜሪካ ህግ አውጪ አካል የሃገሪቱ መንግስት በኢትዮጵያ ላይ የውሳኔ ሃሳብ እንድያጸድቅ እያካሄደ ያለው እንቅስቃሴ ተቀባይነት እንዲያገኝ አለም አቀፍ ዘመቻ በማካሄድ ላይ መሆኑን አምነስቲ ኢንተርናሽናል ገለጸ።
አለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቱ የዘመቻው አካል የሆነና በኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩር መድረክ ሰኞ በዚህ በአሜሪካ ኒው ዮርክ ከተማ መካሄዱ ታውቋል።
በሃገሪቱ ተግባራዊ ተደርጎ የሚገኘው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተከትሎ በኒው ዮርክ ከተማ በተካሄደው የውይይት መድረክ በርካታ አለም አቀፍ ተቋማትና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ግለሰቦች ተሳታፊ መሆናቸውን አምነስቲ ኢንተርናሽናል ገልጿል።

የመድረኩ አስተባባሪ የነበሩት ስቲቭ ላቲመር ((Steve Latimer) የውይይት መድረኩ በኢትዮጵያ እየተፈጸሙ ያሉ ግድያዎችና መሰረታዊ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ለአለም አቀፍ ማህበረሰብ ልዩ ቱኩረት እንዲያገኝ መዘጋጀቱን አስረድተዋል።
የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቱ እየተካሄደ ያለው ይኸው እንቅስቃሴ የአሜሪካን ህግ አውጪ አካል የአሜሪካ መንግስት በኢትዮጵያ ላይ ጠንካራ የተባለ ውሳኔን እንዲያስተላልፍ እያካሄደ ያለውን ዘመቻ ለማገዝ እንደሆነ ስቲቭ ላቲመር ለመገኛና ብዙሃን አስታውቀዋል።
በአሜሪካ የምክር ቤት አባላት እየተካሄደ ያለውና እንዲጸድቅ ከተለያዩ ወገኖች ግፊት እየተደረገው ያለው የውሳኔ ሃሳብ አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ዘርፈ ብዙ ግንኙነት እንድትመረምር ይጠይቃል።
ይህንኑ ዘመቻ እያካሄዱ ያሉት የአሜሪካ የምክር ቤት አባላት አሜሪካ ለኢትዮጵያ መንግስት የምትሰጠውን ወታደራዊ እንዲሁም ዲፕሎማሲያዊ ድጋፍ እንድታጤነው ባቀረበው ሰነድ አስፍሯል።
በኒው ዮርክ ከተማ ሰኞ ምሽት በተካሄደው የውይይት መድረክ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እንዲሁም የኢትዮጵያ መንግስት የጸጥታ ሃይሎች ይወስዱታል የተባለው የሃይል እርምጃ መወያያ አጀንዳ ሆኖ መቅረቡን ለመረዳት ተችሏል።
ለአንድ አመት ያህል በኦሮሚያ በቅርቡ በአማራ ክልሎች በተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ ከ800 በላይ ሰዎች መገደላቸውን አምነስቲ ኢንተርናሽናል ይገልጻል።
አሜሪካንን ጨምሮ የአውሮፓ ህብረትና የተለያዩ አካላት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ስጋት አሳድሮባቸው እንደሚገኝ በተደጋጋሚ ሲያስታውቁ ቆይተዋል።

No comments:

Post a Comment