Tuesday, October 25, 2016

አዲስ ስታንዳርድ መጽሄት ህትመት ማቋረጡን አስታወቀ

ኢሳት (ጥቅምት 15 ፥ 2009)
በኢትዮጵያ ተግባራዊ ተደርጎ የሚገኘው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በሃገሪቱ በሚታተሙ የመገናኛ ብዙሃን ውጤቶች ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ በማሳደሩ ምክንያት ህትመት ለማቆም መገደዱን አዲስ ስታንዳርድ መጽሄት ይፋ አደረገ።
ከአስር አመት በፊት በንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ተመዝግቦ በወር አንድ ጊዜ ለህትመት ይበቃ የነበረው መጽሄቱ በመንግስት የወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስራውን እንዳይቀጥል ማድረጉን የመጽሄቱ መስራችና ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጸዳለ ለማ ለዜና ክፍላችን አስታውቃለች።
በእንግሊዝኛ ቋንቋ ሲታተም የቆየው አዲስ ስታንዳርድ መጽሄት በተለይ በኦሮሚያ ክልል ሲካሄድ የቆየውን ህዝባዊ ተቃውሞ ስፊ ዘገባን በመስጠት ሲዘግብ መቆየቱ ይታወሳል።
ይሁንና መጽሄቱን ተግባራዊ ተደርጎ በሚገኘው በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ስራውን መቀጠል እንዳልቻለና የማይቻል አስቸጋሪ ደረጃ ውስጥ መግባቱን አዘጋጇ አስረድታለች።
የመንግስት ማተሚያ ቤቶች የህትመት ውጤታቸውን ለማሳተም ወደ ድርጅቱ ሲሄዱ ከኮማንድ ፖስቱ ፈቃድ እንዲያመጡ ይጠይቁ እንደነበር ህትመቱን ለማቆም የተገደደው የአዲስ ስታንዳርድ መጽሄቱ አዘጋጆች ገልጻለች።
መንግስት በማተሚያ ቤት በኩል እየፈጸመ ካለው ወከባ በተጨማሪ የህትመት ውጤቶችን የሚሸጡ ግለሰቦችንና የንግድ ድርጅቶች ጋዜጦችንና መጽሄቶችን ለመረከብ ፍራቻ አድሮባቸው እንደሚገኝም ታውቋል።
መጽሄቱ በአዋጁ ምክንያት ከህትመት ሲወጣ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲሆን የተለያዩ አበይት ጉዳዮችን ግን በኦንላይን ህትመቱ እንደሚቀጥል አስታውቋል።
የዚሁ አዋጅ መውጣት ተከትሎ በሃገሪቱ የሚታተሙ የመገናኛ ብዙሃን ውጤቶች ጋዜጦችን ማሳተም አስቸጋሪ እየሆነባቸው መምጣቱን ሲገልፁ መቆየታቸው ይታወሳል። ተግባራዊ ተደርጎ የሚገኘው አዋጅ የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች በማንኛውም አካል ላይ አስፈላጊውን እርምጃ እንዲወስዱ ስልጣንን ሰጥቷል።
ያለ-ፍርድ ቤት ትዕዛዝ የቤት ለቤት ፍተሻ እንዲካሄድ የደነገገው አዋጁ፣ በመገናኛ ብዙሃን ውጤቶች ላይ ቁጥጥር እንዲካሄድ ውሳኔን አስተላልፏል።
የአዋጁ መውጣትን ተከትሎ የኢንተርኔት አገልግሎት እንዲቋረጥ የተደረገ ሲሆን ሰዎች ለሚሰጧቸው አስተያየቶች ተጠያቂ እንደሚሆኑም ተደንግጓል። የጋዜጠኛ መብት ተማጋች ድርጅቶች አዋጁ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን አፍኖ እንደሚገኝ በመግለጽ ላይ ናቸው።
መቀመጫውን በዚህ በአሜሪካ ያደረገው ኮሚቴ ቱ ፕሮቴክት ጆርናሊስት (CPJ) ኢትዮጵያ በአለማችን በመገናኛ ብዙሃን ላይ አፈና ከሚያካሄዱ 10 ዋነኛ ሃገራት መካከል አንዷ መሆኗን ይገልጻል።
በሃገሪቱ ተግባራዊ ተደርጎ የሚገኘው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሁሉንም የመረጃ መለዋወጫ መንገዶች በመዝጋት ጋዜጠኞችንና ጦማሪያንን አደጋ ውስጥ ከቶ እንደሚገኝ ሰኞ ባወጣው መግለጫ አስተውቋል።

No comments:

Post a Comment