Tuesday, October 25, 2016

በኢትዮጵያ መንግስት የተፈጸመ የኢንተርኔት የስለላ ተግባር ክስ መቀጠል ይገባዋል ሲል አንድ ድርጅት ገለጸ

ኢሳት (ጥቅምት 15 ፥ 2009)
በአንድ አሜሪካዊ ዜጋ ላይ በኢትዮጵያ መንግስት የተፈጸመ የኢንተርኔት የስለላ ተግባር ክስ መቀጠል ይገባዋል ሲል ጉዳዩን በመከታተል ላይ የሚገኘው ድርጅት ይግባኝ አቀረበ።
ኤሌክትሮኒክስ ፍሮንቲየር ፋውንዴሽን የተሰኘውና የስለላ ድርጊቱ የተፈጸመባቸውን አቶ ኪዳኔን ጉዳይ በመከታተል ላይ የሚገኘው ድርጅት የኢትዮጵያ መንግስት ለፈጸመው የስለላ ድርጊት ተጠያቂ መሆን ይገባዋል ሲል ይግባኙን ዋሽንግተን ዲሲ ከተማ ለሚገኝ የይግባኝ ፍርድ ቤት አቅርቧል።

ይኸው የክስ ሂደት ከሁለት አመት በፊት በተመሰረተ ጊዜ ድርጊቱን ማስተባበል ያልቻለው የኢትዮጵያ የመንግስት የኢንተርኔት የስለላ ድርጊቱ መነሻው በአሜሪካ ምድር ስላልሆነ ያለመከሰስ መብት አለኝ ሲል ሲከራከር መቆየቱ ይታወሳል።
ይሁንና በከፍተኛ ፍ/ቤት ቀርቦ የክስ ሂደቱ ተስተጓጉሎ የሚገኘው ክስ መቀጠል ይኖርበታል ሲል አሜሪካዊ ዜጋውን ወክሎ ክሱን የሚከታተለው ተቋም ለይግባኝ ፍ/ቤቱ አቤቱታውን አቅርቧል።
መቀመጫቸውን በውጭ አገር ያደረጉ ተቋማት የአሜሪካዊ ዜጎችን መብት በዚህ መልኩ በጣሱ ጊዜ ድርጊቱን በፈጸመ አካላት ላይ ክስ እንዲመሰረት ተበዳዮች ፈቃድ ማግኘት ይኖርባቸዋል ሲል የድርጅቱ ሃላፊ ሲንዲ ኮህን IB-Times ለተሰኘ የቴክኖሎጂ መጽሄት አስረድተዋል።
መንግስት በሚሊዮን የሚቆጠር ዶላርን በማፍሰስ መቀመጫውን በጣሊያን ካደረገ የቴክኖሎጂ ኩባንያ የኢንተርኔት የስለላ ድርጊትን ለመፈጸም የሚያስችሉ አገልግሎቶች በመግዛት ድርጊቱን ሲፈጽም እንደነበር ይፋ መደረጉ ይታወሳል።
የስለላ ድርጊቱን ያጋለጠው አንድ የካናዳ የቴክኖሎጂ ኩባንያ የኢትዮጵያ መንግስት አገልግሎቱን ከተፈቀደለት ተግባር ውጭ በመጠቀም በውጭ ሃገር ያሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና ጋዜጠኞችን የግል የኤሌክትሮኒክስ ቁሳቁሶች ሲሰልል መቆየቱን ይፋ አድርጓል።
የመጀመሪያውን መውጣት ተከትሎም አገልግሎቱ ሲያቀርብ የነበረ አንድ የጣሊያን የሃኪኢንግ ተቋም ድርጊቱ ከድርጅቱ ዕውቅና ውጭ ለሰብዓዊ መብት ጥሰት መዋሉን አረጋግጦ የተፈጸመውን የስለላ ተግባር ተቃውሟል።
በአንድ አሜሪካዊ ዜጋ ላይ የተፈጸመው የስለላ ተግባር ወደ ፊት በሌሎች ዜጎች ላይ ሊቃጣ የሚችል ስጋት በመሆኑ የይግባኝ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን ተመልክቶ ክሱ እንዲቀጥል ውሳኔ እንዲሰጠን እንጠይቃለን ሲል አሜሪካዊውን ወክሎ የሚገኘው ተቋም በይግባኙ አስፍሯል።
የይግባኝ ፍርድ ቤቱም በቀረበለት ጥያቄ ላይ በቅርቡ ብይኑን ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል።

No comments:

Post a Comment