Monday, February 6, 2017

የቅዱስ ላሊበላ አቢያተ-ክርስቲያናት አስተዳደሪ ቆሞስ አባ ወልደተንሳይ አባተ በመንግስት ጣልቃገብነት ከሃገር መሰደዳቸውን ገለጹ

ኢሳት (ጥር 29 ፥ 2009)

የታሪካዊው ቅዱስ ላሊበላ አቢያተ-ክርስቲያናት አስተዳደር የነበሩት ቆሞስ አባ ወልደተንሳይ አባተ በመንግስት ጣልቃገብነት ከሃገር መሰደዳቸውን ገለጹ። የላሊበላ አብያተክርስቲያናት ሰበካ ጉባዔ በመንግስት ባለስልጣናትና በብአዴን ካድሬዎች ቁጥጥር ስር መውደቁንም ለኢሳት በሰጡት ቃለምልልስ አመልክተዋል።
ወልቃይት የትግራይ ነው በሚል ለህዝቡ እንዲያስተምሩ ግፊት ይደረግባቸው እንደነበርም አመልክተዋል። በመጨረሻም ምክንያቱ ባልታወቀና ባልተገለጸ መንገድ በስፍራቸው ሌላ ሰው ተሹሞ መገኘቱን ገልጸዋል።

መልአከ ጸሃይ ቆሞስ አባወልደተንሳዬ አባተ ታሪካዊው ላሊበላ ቤተከርስትያን በዩኔስኮ የተመዘገባ የአለም ቅርስ ቢሆንም፣ ለአደጋ የተጋለጠበት ሁኔታ መኖሩን አስረድተዋል።
የውቅር አብያተ ክርስቲያናቱን ደህንነት ለመጠበቅ በሚል በመከለያነት የተቀመጠው ብረት ከባድ በመሆኑ፣ ጉዳት ያደርሳል በሚል ስጋት ያቀረቡት አቤቱታ ሰሚ አለማግኘቱንም ገልጸዋል።
የሃይማኖቶች ጉባዔ በሚል የተዋቀረውና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ አቡነ ማቲያስ የሚመራው ኮሚቴ መንግስት እንዳዋቀረው የሚገለጹት ቆሞስ አባ ወልደትንሳዔ አባተ አመራሩን በትክክል የያዙት የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትሩ ዶ/ር ሽፈራው ተክለማሪያም አሁን ደግሞ አቶ ካሳ ተክለብርሃን መሆናቸውን በመግለጽ ተቋሙ የመንግስት ጉዳይ አስፈጻሚ ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክስርቲያን ቁልፍ ስፍራዎችን የተቆጣጠሩት የህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ታጋዮች መሆናቸውን የገልጹት ቆሞስ አባ ወልደትንሳዔ አባተ ህዝብን ለማሳሳት ለሰዎቹ የክህነት ማዕረግ እንደተሰጣቸውም አስረድተዋል።

No comments:

Post a Comment