Friday, February 3, 2017

የኢትዮጵያ መንግስት የ26.5 ቢሊዮን ብር ቦንድ ሽያጭ አጸደቀ



ኢሳት (ጥር 2009)

የኢትዮጵያ መንግስት ያጋጠመውን የፋይናንስ እጥረት ለመቅረፍ የ26.5 ቢሊዮን ብር ቦንድ ሽያጭ እንዲካሄድ ያቀረበው ጥያቄ ረቡዕ በፓርላማ ጸደቀ።
የምጣኔ ሃብት ባለሙያዎች በበኩላቸው ሊካሄድ የታሰበው የቦንድ ሽያጭ የሃገሪቱን አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት ሊያባብስ ይችላል ሲሉ ስጋታቸውም ገልጸዋል። በፓርላማ የጸደቀው ይኸው አዋጅ መንግስት ከተለያዩ አካላት ወለድ የሚከፈልበት የቦንድ ሽያጭ እንዲያከናውን ይሁንታ መስጠቱ ታውቋል።
የአዋጁ መፅደቅን ተከትሎ መንግስት ከተለያዩ አበዳሪ የፋይናንስ ተቋማት በረጅም ጊዜ የሚከፈል የ26.5 ቢሊዮን ብር የቦንድ ሽያጭ ያካሄዳል ተብሎ ይጠበቃል።
ሊካሄድ የተወሰነው የቦንድ ሽያጭ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ካፒታል ለማሳደግ ያለመ እንደሆነ የመንግስት ባለስልጣናት ቢገልጹም የምጣኔ ሃብት ባለሙያዎች ዕርምጃ ሃገሪቱ ያጋጠማትን የበጀትና የፋይናንስ እጥረት ለመታደግ እንደሆነ አስረድተዋል።

ሃገሪቱ በከፍተኛ ዕዳ ውስጥ እያለች ሊካሄድ የተወሰነው የቦንድ ሽያጭ የመንግስት ዕዳ እንዲጨምር በማድረግ የዋጋ ግሽበት እንዲባባስ አስተዋፅዖ ሊያደርግ እንደሚችል የምጣኔ ሃብት ባለሙያዎች ይገልጻል።
ከተለያዩ የፋይናንስ ተቋማት ይቀርባል ተብሎ የሚጠበቀው ይኸው ከፍተኛ ገንዘብ የአምስት አመት የእፎይታ ጊዜ ተቀምጦለት በአስር አመት ውስጥ ሊከፈል የታሰበ እንደሆነም የቦንድ ሽያጭ መመሪያው ያመለክታል።
ይሁንና መንግስት የቦንድ ሽያጩን ለረጅም ጊዜ የሚከፈል አድርጎ ማስቀመጡ የፋይናንስ ተቋማት በገንዘብ አቅርቦታቸው ላይ ከፍተኛ ወለድ እንዲጠይቁ የሚያደርግ መሆኑን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው አካላት አስረድተዋል።
እንደፈረንጆቹ አቆጣጠር 2015 አም መገባደጃ ድረስ የኢትዮጵያ አጠቃላይ የብድር መጠን ወደ 36 ቢሊዮን ዶላር አካባቢ ደርሶ እንደነበር በተለያዩ የፋይናንስ ተቋማት ይፋ መደረጉ ይታወሳል።
የአለም ባንክን ጨምሮ የተለያዩ የፋይናስ ተቋማት ሃገሪቱ ያለባት የብድር ክምችት በኢኮኖሚ እድገቱ ላይ ተፅዕኖን እያሳደረ ነው በማለት መንግስት የማስተካከያ ዕርምጃን እንዲወስድ አሳስበዋል።
የሃገሪቱ የውጭ ንግድ ገቢ እያሽቆለቆለ ባለበት ወቅት የእዳ ክምችቱ መጨመር በኢኮኖሚ ዕድገቱ ላይ ከሚያሳድረው ተፅዕኖ በተጨማሪ የብር የመግዛት አቅም እንዲዳከም ማድረጉን የምጣኔ ሃብት ባለሙያዎች ይገልጻሉ።
በኢትዮጵያ ተከስቶ ያለውን ይህንኑ የፋይናንስ ቀውስ ተከትሎ የብር የመግዛት አቅም መዋዠቅን በማሳየት ላይ ሲሆን፣ የአለም ባንክ ችግሩን ለመቅረፍ ብር ከዶላር ጋር ያለው የመግዛት አቅም እንዲቀንስ ሃሳብ አቅርቧል።
መንግስት በበኩሉ ሃሳቡን ተግባራዊ ማድረግ ከጥቅሙ ጉዳቱ ይበልጣል በማለት ሃሳቡን እንደማይቀበል ይገልጻል። የባቡር አገልግሎት፣ የስኳር እና የሃይል መመንጫ ፕሮጄክቶች ለመንግስት የእዳ ክምችት አስተዋጽዖ ካደረጉ መካከል ዋነኞቹ ሆነዋል።
ባለፈው ሳምንት የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የብድር ዕዳው ከ100 ቢሊዮን ብር በላይ መድረሱን ይፋ ማድረጉ የሚታወስ ሲሆን፣ የባቡር አገልግሎቱ ሙሉ ለሙሉ ስራውን ሳይጀምር ብድር የመክፈያ ጊዜው እንደተቃረበበት ተመልቷል።
ይሁንና መንግስታዊ ድርጅቱ ብድሩን በምን መልኩ እንደሚከፍል ግራ ተጋብቶ እንደሚገኝ አስታውቋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲሁም በፋይናንስ እትረት ምክንያት የፕሮጄክቶች ስራ መጓተተ እንዳጋጠማቸው በቅርቡ ለፓርላማ ባቀረበው ረኢፖርት አስረድቷል።

No comments:

Post a Comment