Wednesday, January 25, 2017

በኩዌት አንድ ኢትዮጵያዊትን ጨምሮ ሰባት የተለያዩ አገር ዜጎች በስቅላት ተቀጡ

ኢሳት (ጥር 17 ፥ 2009)
የኩዌትት መንግስት አንድ ኢትዮጵያዊትን ጨምሮ ሰባት የተለያዩ ሃገራት ዜጎችን ዛሬ ረቡዕ በስቅላት የሞት ቅጣት መፈጸሙን የሃገሪቱ ዜና አገልግሎት ኩና ዘገበ።
ከአንድ ኢትዮጵያዊት በተጨማሪ ሁለት የኩዌት፣ ሁለት የግብፅ፣ አንድ የባንግላዴሽ፣ እና አንድ የፊሊፒንስ ዜጋ በግድያ፣ በአስገድዶ መድፈር፣ እንዲሁም ሰዎችን በማገት ድርጊት ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው ድርጊቱ ሊፈጸምባቸው መቻሉን የኩዌት መንግስት ለመገናኛ ብዙሃን ገልጸዋል።

ስሟ ያልተገለጸው ኢትዮጵያዊትና ሌላ አንድ የፊሊፒንስ ዜጋ በአሰሪዎቻቸው ላይ ግድያን በመፈጸማቸው ምክንያት የሞት ቅጣቱ እንደተላለፈባቸው የኩዌት ዜና አገልግሎት የሃገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ቻርለስ ጆሴን ዋቢ በማድረግ በዘገባው አስፍሯል።
የኩዌት መንግስት ከአራት አመት በኋላ የስቅላት ድርጊት ሲፈጸም ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑ የተነገረ ሲሆን፣ ከሰባቱ መካከል አንደኛው የኩዌት ዜጋ የሃገሪቱ የንጉሳዊያን የቤተሰብ አባል መሆኑም ተመልክቷል።
ሼክ ፈይሳል አብደላህ አልጃብር የተባለው ይኸው ግለሰብ ግድያን በማቀነባበርና ህገወጥ መሳሪያን በመታጠቅ ክስ ተመስርቶበት በእስር ላይ እንደነበር የኩዌት ዜና አገልግሎት በዘገባው አስነብቧል።
ከኢትዮጵያዊቷ ጋር አሰሪዋን ገድላለች ተብላ የሞት ቅጣት የተላለፈባትን ጃካቲያ ፓዋን ለማስለቀቅ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ሲያደርግ ቢቆይም ድርድሩ ሊሳካ አለመቻሉን የኩዌት ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።
የፊሊፒንስ ተወላጅ የሆነችው ፓዋ፣ ረቡዕ ጠዋት ስቅላቱ ከመፈጸሙ በፊት ቤተሰቦቿን በስልክ እንድታነጋገር ተፈቅዶላት የነበረ ሲሆን፣ በዚሁ የስልክ ንግግር ወድሟን ያገኘችው ፓዋ የሁለት ልጆቿን ጉዳይ አደራ እንደሰጠች አሶሼይትድ ፕሬስ ዘግቧል።
በተመሳሳይ የወንጀል ድርጊት የሞት ቅጣት የተላለፈባት ኢትዮጵያዊት፣ ማንነቷ ካለመገለጹ በተጨማሪ፣ ቤተሰቦቿን የማግኘት ዕድል ተሰጥቷት ይሁን አይሁን የተገለጸ ነገር የለም።
ከዚሁ የሞት ቅጣት ከተፈረደባቸው አንዷ የነበረችው የኩዌት ተወላጅ ከሰባት አመት በፊት ባሏ ሁለተኛ ሚስቱን ባገባ ጊዜ ለዝግጅቱ በተጣለ ድንኳን ላይ የእሳት ቃጠሎ አድርሳ ለ57 ሰዎች ሞት ምክንያት እንደነበር የኩዌት ዜና አገልግሎት በዘገባው አክሎ አመልክቷል።
የኢትዮጵያዊቷን ቅጣት በተመለከተ የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የሰጠው ምላሽ የለም።

No comments:

Post a Comment