Tuesday, January 24, 2017

የአፍሪካ ቀንድ የሰብአዊ መብት ሊግ ባወጣው መግለጫ ካለፈው አመት ጥቅምት ወር ጀምሮ በኦሮምያ 1200 ሲገደሉ፣ ከ70 ሺ በላይ የሚሆኑት ደግሞ ታስረዋል

ጥር ፲፮ ( አሥራ ስድስት )ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የአፍሪካ ቀንድ የሰብአዊ መብት ሊግ ባወጣው መግለጫ ካለፈው አመት ጥቅምት ወር ጀምሮ በኦሮምያ 1200 ወጣቶች፣ እናቶችና አባቶች ሲገደሉ፣ ከ70 ሺ በላይ የሚሆኑት ደግሞ ታስረዋል።
በሺዎች የሚቆጠሩ መሰደዳቸውን እንዲሁም በርካታ ሴቶች በአጋዚ ወታደሮች መደፈራቸውንም የሰብአዊ መብት ድርጅቱ ገልጿል። በታሃድሶ ስልጠና ስም በርካቶች ወደ ጦላይ፣ ሁርሶ እና ዲዴሳ ካምፖች መወሰዳቸውን የገለጸው ድርጅቱ፣ በእነዚህ ካምፖች በርካቶች በአሰቃቂ ሁኔታ ተደብድበው ህይወታቸው አልፏል። ይህ አልበቃ ብሎ የሶማሊ ልዩ ሃይል ሚሊሺያዎች በኦሮሞ ዜጎች ላይ ተጨማሪ ግድያዎችን እየፈጸሙ ነው ብሎአል። ባለፈው አንድ ወር ልዩ ሃይሉ የሚፈጽመው ግፍ እየጨመረ መምጣቱን የሚገልጸው ድርጅቱ፣ ልዩ ሃይሉ በጉርሱም፣ ኩንቢ፣ ባቢሌ፣ ቺክሳን፣ ሊባን ፣ ላጋ ዳዋ ፣ ፉናንጋርሱ፣ ኢለሌ ከ150 በላይ ሰዎችን ገድሏል። የአለማቀፍ ማህበረሰብ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ ምርመራ እንዲደረግም ጠይቋል። የሶማሊ ልዩ ሃይል በኦሮምያ ብቻ ሳይሆን በሶማሊ ክልል ነዋሪዎች ላይ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት በመፈጸም ይወነጀላል። ልዩ ሃይሉ የሚመራው በክልሉ ፕሬዚዳንት ነው። የህወሃት ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዦች ከክልሉ ፕ/ት ጀርባ በመሆን ግድያዎችን እንደሚያቀነባበሩ በተደጋጋሚ ተዘግቧል። የአፍሪካ ቀንድ የሰብአዊ መብት ሊግም፣ ከጥቃቱ ጀርባ የህወሃት ወታደራዊ አዛዦች እጅ እንዳለበት ጠቅሷል።

No comments:

Post a Comment