Wednesday, April 15, 2015

ሞያሌ ከትናንት ምሽት እስከ ዛሬ እኩለቀን ድረስ በተኩስ ተናጠች

ሚያዝያ ፮(ስድስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የከተማዋ የኢሳት የመረጃ ምንጮች እንደገለጹት ከትናንት ሰኞ ምሽት ጀምሮ እስከ ዛሬ ማክሰኞ እኩለቀን ድረስ ከተማዋ በተኩስ ስትናወጥ ውላለች።
አንዳንድ ነዋሪዎች እንደሚሉት የተኩሱ ልውውጡ የተካሄደው በመከላከያ ሰራዊት አባላት እና በሶማሊ ክልል ልዩ ሚሊሺያዎች መካከል ነው፡፡ የመከላከያ ሰራዊት አባላት አንድ የክልል 5 ጠባቂ መግደላቸውን ተከትሎ፣ የክልሉ ልዩ ሃይል ሚሊሺያዎች በየሰዎች ቤት እየገቡ እቃዎችን ከመሰባበርና ከመዝረፍ በተጨማሪ ከተማዋን በተኩስ ሲበጠብጡዋት አድረዋል።
ጧት አካባቢ በአማርኛ ፣ በኦሮምኛና በሶማሊኛ የተጻፉ ወረቀቶች መበተናቸውን የሚገልጹት ነዋሪዎች፣ ጽሁፎቹ በከተማው ያሉትን ባንዶች ለመቅጣት መጥተናል የሚል ይዘት እንዳለው ነዋሪዎች ተናግረዋል። በማግስቱ ለገዢው ፓርቲ ቅርበት አላቸው የሚባሉ ድርጅቶች ጥቃት ደርሶባቸዋል።
አንዳንድ ወገኖች እንደሚሉት የሶማሊ ክልል ተጣቂዎች ምሽት ላይ ሁለት የመከላከያ ሰራዊት አባላትን አስቁመው በሚፈትሹበት ጊዜ፣ አንደኛው ለምን ትፈትሹታላችሁ በማለት ፈታሹን የገደለው ሲሆን፣ መረጃው በሶማሊ ክልል ታጣቂዎች ዘንድ በመድረሱ የበቀል እርምጃ ለመውሰድ መነሳሳታቸውን ነዋሪዎች ገልጸዋል።
የክልሉ ታጣቂዎች ሌሊት ላይ በወሰዱት እርምጃ ከገዢው ፓርቲ ጋር ግንኙነት አላቸው ተብለው የሚጠረጠሩ የንግድ ድርጅቶች ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸዋል። ማክሰኞ ጠዋት ደግሞ የከተማዋ የሶማሊ ተወላጆች የመከላከያን ድርጊት በመቃወም ወደ አደባባይ የወጡ ሲሆን፣ በመኪኖች እና በተለያዩ ድርጅቶች ላይ ባደረሱት ጥቃት ከፍተኛ ጉዳት ደርሶአል። የፌደራል ፖሊሶች ተከታታይ ጥይቶችንና አስለቃሽ ጪስ በመተኮስ ተቃውሞውን ለመቆጣጠር ቢችልም፣ ውጥረቱ እስከ ምሽት ዘልቋል። ትምህርት ቤቶች፣ የመንግስት መስሪያ ቤቶች እና የንግድ ድርጅቶች ተዘግተው ውለዋል።
የፌደራል ፖሊስ አባላት ከረብሻው ጋር እጃቸው አለበት ብለው የሚጠረጥሩዋቸውን ሰዎች ይዘው በማሰር ላይ ናቸው።


No comments:

Post a Comment