Wednesday, April 29, 2015

ኤዶምንና ማህሌትን ብቻ ሳይሆን የ45 ሚሊዮን ሴቶች ክብርን ነው ያቀለሉት – ግርማ ካሳ

ኤዶም ካሳዬ ጋዜጠኛ ናት። ማህሌት ፈንታሁን ደግሞ «ሰለሚያገባን እንጦምራለን» በሚል የአለም አቀፍም ሆነ የኢትዮጵያ ሕገ መንግስት በሚፈቅድላቸው መሰረት፣ ብሎግ ከሚያደርጉ ዞን ዘጠኞች አንዷ ናት። ኤዴሞም ሆነ ማህሌት የጻፉት፣ የተናገሩት የተደበቀም ሆነ የተሸፈነ ነገር የለም። ለፍትህ ከመቆማቸው በቀር ያጠፉት ጥፋት የለም። ወንጀላቸው አገራቸውን መዉደዳቸው ነው። ሆኖም ሕወሃት «ሽብርተኞች» ብሎ ካሰራቸው ይኸው አንድ አመት ሆናቸው። ቢያንስ ከ27 ጊዜ በላይ ፍርድ ቤት ተመላልሰዋል። አስቡት በአንድ አመት ዉስጥ ቢያንስ 27 ጊዜ !!!!!

የአገሪቷ ሕገ መንግስት በማረሚያ ቤት ያሉ እስረኞች በምን መልኩ መያዝ እንዳለባቸው በግልጽ አስቀምጧል። በአንቀጽ 19 ንኡስ አንቀጽ አንድ ላይ፣ እያንዳንዱ ዜጋ ፣ እስረኞችን ጨምሮ፣ ኢሰብአዊ ፣ ጭካኔ የተሞላባቸዉና ክብርን የሚነኩ ቅጣቶች ሊቀበል እንደማይገባ ያስቀምጣል። ሆኖም ረእቡ ሚያዚያ 14 ቀን፣ የአዲስ አበባ ሰልፈኞች እንዳሉት፣ ለሕወሃት ሕገ መንግስቱ ወረቀት ብቻ ነው። እህቶቻችን ሞራላዊ፣ መንፈሳዊና የሴትነት ክብራቸውን በመድፈር ፣ ራቁታቸውን ሆነው በአረመኔ የሕወሃት ወንድ ምናምንቴዎች ፊት ስፖርት እንዲሰሩ መገደዳቸው ምን ያህል እንደ አገር መዝቀጣችንን የሚያሳይ ነው። በርግጥ ኤዶምና ማህሌትን ብቻ ሳይሆን ሕወሃቶች ከ40 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑትን የአገራችንን እናቶችና እህቶች ነው የደፈሩት።


ለሰብአዊ መብት ጉባኤ ኮሚሽን፣ ኤዶም ላሳዬና ማህሌት ፋንታሁን ከተናገሩት የተወሰነውን እንሆ፡

«ሙሉ ልብሴን እንዳወልቅ ተገድጄ ራቄቴን በወንድ መርማሪዎች ፊት ስፓርት አንድሰራ እገደድ ነበር ፡፡ “ሴትነትሽ አንዲህ ከሚዋረድ አመጽ እንዳነሳሳሽ እመኚ ተብያሁ”»

ማህሌት ፋንታሁን
«በተለምዶው ከምመረመርበት ቢሮ ውጩ አንደኛ ፎቅ አዳራሽ ውስጥ ለምርመራ ተወስጄ ልብሴን እንዳወልቅ እና የተለያዬ ለመናገር የሚከብዱ ስፓርታዊ አንቅስቃሴዎችን እንድሰራ ተገድጃለሁ፡፡ እንዲህ ከምትዋረጂ አመጽ ልናስነሳ ነበር ብለሽ ለምን አታምኚም እያለ ይመታኝ ነበር »
ኤዶም ካሳዬ

እንግዲህ የዛሬይቱ የሕወሃት ኢትዮጵያ ይች ናት። ይህ አይነቱን ኢሰብዊነት ማስቆም ካልቻልን እንደ አገር ሆነ እንደ ሕዝብ መቀጥል አንችልም። እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ፣ ይህ አይነቱ ብሄራዊ ዉርድት እንዲቆም መነሳት አለበት። ፈረንጆችን እንደሚሉት “We have to claim back our country from these monsters” ። በተለይም እናቶችና እህቶች ፣ አዉቃለሁ ብዙ ግርግር አትወዱም። ግን አሁን እናንተም ከወንዱ ባልተናነሰ የምትነሱበት ጊዜ ነው።


No comments:

Post a Comment