Friday, February 20, 2015

ለቅሶ በራፍ ፍርድ ቤት ( የልጅና የአባት መተያየት) – ለገሰ ወልደሃና

ዘመነ ምህረት እና መለሰ መንገሻ ከተያዙ አንድ ወር ከአንድ ቀን ሆናቸው በዛሬው እለት ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎ የመኢአድ አባላት እና ይህ በፎቶ የምታዩት አንድነት ዘመነ ከእናቱ ጋር ከሰሜን ጎንደር ሌሎችም የዘመነ ቤተሰብም ተገኝተዋል ዘመነ የመኢአድን ጠቅላላ ጉባኤ ተካፍሎ ከተመለሰ በኋላ አላገኘነውም አይኑን ለማየት ጉጉተናል የተባለው ሰአት 8:00 ደረሰና ከእሱ ጋር የታሰረው መለሰ መንገሻም አብረው በጋቴና ሌሎች ወደ 25 የሚጠጉ ወጣቶች በፓሊስ ታጅበው ገቡ በእርቀት እጃችን በማወዛወዝ ሰላም አልናቸው እነሱ ባልታሰረው እጃቸው መለሱልን ። በጣም ተጎሳቁለዋል በተለይ መለሰ ግርጥት ብሏል፤ተአምረኛው አንድነት ።

አንድነት የዘመነ የበኩር ልጅ ነው። እድሜውም 3 አመት ከአራት ወር ነው። ሲበዛ ያሳዝናል ። አባቱ ዘመነ፣ ከበርካታ ታሳሪዎች ጋር ወደ ፍርድ ቤት ሲገባ አባቱን ያየው አንድነት፣ ከእጄ አምልጦ ወደ አባቱ ሮጠ። አባቱን ግን አላገኘም። አባቱን ለማቀፍ የሮጠው ልጅ፣ ከፓሊሱ አልፎ አባቱን ሊያቅፍ አልቻለም። ቀድሞም ይህ ህጻን አይኑ እያየ አባቱን እየደበደቡ የወሰዱት ፓሊሶች ነበሩና የማይጋፋው ጉልበተኛ እንደገጠመው አውቋል።



ያችን ቅጽበት ሁሌ የምረሳው አይደለም። አንድነት አራዳን በጩኸት አቀለጣት። ዘመነን ለማየት የጓጓው አይናችን ዘመነን እረሳ። ተሸነፍን። እንባችን ግድቡን ጥሶ ፈሰሰ። አንዳንድ የመኢአድ አባላት በህጻኑ አንድነት ልባቸው ተነክቶ ድምጻቸው ከፍ ብሎ እስኪሰማ አለቀሱ። በግቢው የነበሩ ባለጉዳዮችም ሲያለቅሱ ተመልክቻለሁ ። እንዴት ልብ ይነካል ።

ዘመነ ምን ተሰምቶት ይሆን ? በዚህ ክስተት መሀል ዘመነን ባይኔ ፈለኩት። ሌሎች ያለቅሳሉ ። ዘመነ ግን ከአይኑ የሚፈስ እንባ የለም የሆነውን አይቷል። እንዴት አንጀቱ ቻለው ? ዘመነ ልጁን እንዴት እንደሚወደው አውቃለሁ ። ዛሬ እንዴት ቻለው? ምን አልባት እንባን ያላየሁት ወደ ውስጥ እያለቀሰ ይሆን ?


No comments:

Post a Comment