Thursday, December 8, 2016

የአውሮፓ ሃገራት ዜጎቻቸው ወደ ሰሜን ጎንደር እንዳይጓዙ አዲስ ማሳሰቢያን አወጡ

ኢሳት (ኅዳር 29 ፥ 2009)
በሰሜን ጎንደር የተለያዩ አካባቢዎች በመንግስትና በግንቦት ሰባት ሃይሎች መካከል የተቀሰቀሰውን ግጭት ተከትሎ የአውሮፓ ሃገራት ዜጎቻቸው ወደ ስፍራው እንዳይጓዙ አዲስ ማሳሰቢያን አወጡ።
ተደጋጋሚ የጉዞ ማሳሰቢያን ሲያወጡ የነበሩት የጀርመንና የቤልጅየም መንግስታት በኢትዮጵያ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ መሻሻልን ቢያሳይም በአማራ ክልል ስር በሚገኙ ሶስት ዞኖች የጸጥታ ስጋት መኖሩን ይፋ አድርገዋል።
ለዜጎቻቸው አዲስ የጉዞ ማሳሰቢያን ያሰራጩት ሁለቱ የአውሮፓ ሃገራት በጸገዴ፣ ምዕራብና የታች አርማጭሆ የሰሜን ጎንደር አካባቢዎች ዜጎቻቸው ጉዞን ከማድረግ እንዲቆጠቡ አሳስበዋል።
የፈረንጆች አዲስ አመት መግቢያን ምክንያት በማድረግ የጀርመንና የቤልጂየም ዜጎች ወደ ኢትዮጵያ በብዛት የሚጓዙ ሲሆን፣ የሁለቱ ሃገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ሁኔታውን ከግምት ውስጥ በማስገባት የጉዞ ማስጠንቀቂያ ማሰራጨታቸውን ዘቮይስ (The Voice) የተሰኘ መፅሄት ዘግቧል።
በቅርቡ የግንቦት 7 ሃይሎች እንዲሁም ራሳቸውን ያደራጁ የነጻነት ሃይሎች በሰሜን ጎንደር ዞን ስር ከመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ጋር ግጭት ውስጥ መግባታቸው ይታወሳል።


ይህንኑ ድርጊት ተከትሎ የብሪታኒያና የአሜሪካ መንግስታት ዜጎቻቸው ወደስፍራው ከመጓዝ እንዲቆጠቡ በድጋሚ አሳስበዋል። ይሁንና ሃገሪቱ በአካባቢው አለ ስለሚሉት የደህንነት ስጋት ዝርዝር መረጃን ከመስጠት ተቆጥበዋል።
የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በቅርቡ በሁለት ወር ዙር ድንበር አቋርጠው የገቡ የግንቦት ሰባት ሃይሎች መማረካቸውንና 15ቱ መሞታቸውን መግለፁ ይታወሳል።
የታጣቂ ሃይሉ አመራሮች በበኩላቸው መንግስት ያስታወቀውን ግጭት አረጋግጠው ደርሷል በተባለው ጉዳይ ዙሪያ መጋነን መስተዋሉን ለኢሳት በሰጡት ቃለ-ምልልስ አስረድተዋል።
ይኸው በሰሜን ጎንደር ዞን ስር በሚገኙ ስፍራዎች ያለው ግጭት መንግስት ተጨማሪ የጸጥታ ሃይል ወደ አካባቢው እንዲያንቀሳቅስ ማስገደዱን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው አካላት ይገልጻሉ።
የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የሃገሪቱ ዜጎች ወደ ኢትዮጵያ ከመጓዝ እንዲቆጠቡ ያወጣውን ማሳሰቢያ ተከትሎ ኢትዮጵያ ቅሬታን ያቀረበች ቢሆንም አሜሪካ ማሳሰቢያዋን ከሶስት ሳምንት በኋላ ማክሰኞች በድጋሚ አውጥታለች።

No comments:

Post a Comment