Thursday, December 1, 2016

ባለፉት 10 ወራት ብቻ ወደ 90ሺ የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን በስደት የመን መግባታቸውን ተመድ ገለጸ

ኢሳት (ኅዳር 22 ፥ 2009)
ባለፉት 10 ወራቶች ብቻ ወደ 90ሺ የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን በስደት የመን መግባታቸውን የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን አስታወቀ።
ጦርነት ዕልባት ወዳላገኘባት የመን የሚሰደዱ ኢትዮጵያውያን ስጋት እንዳደረሰባት የገለጸው ድርጅቱ ባለፈው አመት ተመሳሳይ ወቅት ከ70ሺ የሚበልጡ ኢትዮጵያውያን ወደ ሃገሪቱ ገብተው እንደነበር አውስቷል።

በየመን ያለው የዕርስ በዕርስ ጦርነት ባላገኘበት ወቅት በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን በመሰደድ ላይ መሆናቸውን የገለጸው ድርጅቱ ባለፉት 10 ወራቶች በተመሳሳይ መንገድ 17ሺ ሶማሊያዊያን ስደተኞች ወደ የመን መግባታቸውን እንዳስታወቀ አልጀዚራ የቴሌቪዥን ጣቢያ ዘግቧል።
ኢትዮጵያውያኑና ሶማሊያዊያኑ ከፈታቸው ጦርነት ወዳለበት ሃገር የመሰደዳቸው ሁኔታ በአፍሪካ ቀንድ ያለውን አስከፊ ችግር የሚያመለክት ነው ሲሉ የተባበሩት መንግስታት ባለስልጣናት አስረድተዋል።
ወደየመን በመሰደድ ላይ ያሉት እነዚሁ ስደተኞች ለተለያዩ የሰብዓዊ የመብት ጥሰትና ስቃዮች እየተዳረጉ እንደሚገኝ የተለያዩ አካላት ሲገልጹ ቆይተዋል።
ይሁንና አለም አቀፍ ተቋማት የስደተኞቹ ሁኔታ ዕልባት እንዲያገኝ የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን ቢያካሄዱም በተለይ የኢትዮጵያውያኑ ስደት ረገብ ሊል አለመቻሉ አሳሳቢ መሆኑን የእርዳታ ድርጅቶች በመግለጽ ላይ ናቸው።
በየመን ያለውን የጸጥታ ሁኔታ የተረጋጋ ባለመሆኑን በኢትዮጵያውያኑና በሶማሊያዊያኑ ስደተኞች ላይ የሚደርሰውን ጉዳት በአግባቡ ማወቅ እንዳልተቻለ በየመን የሚገኘው የአለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት (IOM) አስታውቋል።
ወደ የመንና ወደ ተለያዩ ሃገራት በሚደረገው የስደተኞቹ ጉዞ በርካታ ሰዎች ሞት ላይ ሲሆኑ ባለፈው ወር ብቻ ወደ ጅቡቲ በግዳጅ እንዲሰፍሩ በተደረጉ ከ70 በላይ ኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች መካከል ከ20 የሚበልጡ መሞታቸው ይታወሳል።
ከኢትዮጵያ በተለያዩ የድንበር ግዛቶች የሚደረገውን ስደት ለመቆጣጠር መንግስት ቁጥጥርን ቢያደርግም በተለይ የወጣቶች ስደት ሊቀንስ አለመቻሉን መረጃዎች ያመለክታሉ።
በጎረቤት ኬንያ፣ ሶማሊያ፣ ሱዳንና ሶማሊላንድ በርካታ ኢትዮጵያውያን በመሰደድ ላይ መሆናቸውን በስደተኞች ጉዳይ ዙሪያ የሚሰሩ ድርጅቶች ይገልጻሉ።
በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በማላዊ ታንዛኒያና በሌሎች የደቡባዊ አፍሪካ ሃገራት እስር ቤቶች እንደሚገኙም ታውቋል።

No comments:

Post a Comment