Thursday, June 29, 2017

ህወሃት በዶ/ር አዲሱ ገ/እግዚሃብሄር በኩል በአማራ ክልል ፖሊስ አዛዦች ላይ ምርመራ ጀመረ

ሰኔ ፳፪ ( ሃያ ሁለት ) ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ከክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን የደረሰን መረጃ እንደሚያመለክተው በቅርቡ በክልሉ ከታየው ህዝባዊ የለውጥ እንቅስቃሴ በሁዋላ የታየው የፖሊሶች አቋም፣ ለህወሃት ህልውና አደገኛ ነው በሚል እምነት፣ ራሱ በሚመራው ኮማንድ ፖስት አማካኝነት እየገመገመ ስራቸውን እንዲለቁ፣ ወንጀል ስርተዋል እያለ ወደ እስር ቤት እንዲገቡ ካደረገ በሁዋላ፣ አሁን ደግሞ ዋና ዋና በሚባሉት የፖሊስ አዛዦች ላይ በህወሃቱ ዶ/ር አዲሱ ገብረእግዚአብሄር በሚመራው የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ድርጅት አማካኝነት ክስ ለመመስረት እንቅስቃሴ ጀምሯል። የክልሉ ፓሊስ ኮሚሽን ሃላፊዎች ከሆኑት መካከል ዋና ኮሚሽነር ሙሉጌታ ወርቁ እና ረዳት ኮሚሽነር ደስየ ደጀን የተባሉት አዛዦች፣ ሰኔ 19 ቀን 2009 ዓ.ም ከፍትህ ሚኒስቴር ቢሮ በመጣ ደብዳቤ ተጠርተው ሚስጥራዊ የሆነ ምርመራ የተደረገባቸው ሲሆን፣ የምርምራ መዝገብም ተከፍቶባቸዋል። የምርመራ መዝገቡ በ2008 ዓ.ም መጀመሪያ ላይ በቅማንት ማህበረሰብ የራስ አስተዳደር ጥያቄ ጋር የተያያዘ ነው። በወቅቱ
የተነሳውን ችግር ተከትሎ አዛዦቹ ለአማራ ልዩ ሃይል ፓሊስ ትዕዛዝ በመስጠት በቅማንት ማህበረሰብ ላይ ሆን ተብሎ ግድያ እንዲፈፀም አድርገዋል፣ በዚህም ትዕዛዝ ብዛት ያላቸው የቅማንት ማህበረሰብ አባላት የሆኑ አርሶ አደሮች እና የከተማ ነዋሪዎች ላይ እንዲፈጸምባቸው አድርገዋል የሚል ውንጀላ ቀርቦባቸዋል። የምርመራ መዝገቡ እንዲከፈት ህወሃት ዶ/ር አዲሱ በሚመሩት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን በኩል ከፍተኛ ግፊት ሲያደርግ ከርሟል። የክልሉ መስተዳድር ቀደም ብሎ በዶ/ር አዲሱ የቀረበውን የምርመራ ሪፖርት ያልተቀበለው መሆኑን ቢገልጽም፣ ፖሊሶቹን ከምርመራ ሊታደጋቸው አልቻለም። ምንጮች አያይዘው እንደገለጹት ምርምራው በሁለቱ ኮሚሽነሮች ላይ ብቻ ሳይሆን፣ በስም ባልተገለጹ የክልሉ የፖሊስ አዛዦችና የመስተዳድሩ ባለስልጣናት ላይ ይቀጥላል። ለትግራይ ክልል ነዋሪዎች መፈናቀል ተጠያቂ ናቸው በተባሉት ፖሊሶችም ላይ ተመሳሳይ መዝገብ በመክፈት ለህወሃት ታማኝ አይደሉም የተባሉ ፖሊሶችን የመምታት እርምጃው እንደሚቀጥል ምንቾች ገልጸዋል። የምርመራው መዳረሻ ከፍተኛ ችግር እንደሚያስከትል ፣ አሁንም በክልሉ ባለስልጣናት ዘንድ አለመረጋጋትን እየፈጠረ መሆኑን ምንጮች አክለው ገልጸዋል። እርምጃው “ለህወሃት ታማኝነታችንን እንግለጽ” በሚሉና “ህወሃት አብቅቶለታልና ለህወሃት ታዛዥ ሆነን መቀጠል የለብንም” በሚሉት መካከል የተነሳውን ልዩነት ይበልጥ የሚያሰፋው ይሆናል። “ለህወሃት ታማኝነታችንን በመግለጽ እስካሁን በነበረው ግንኙነት እንቀጥል” የሚለው የአቶ ደመቀ መኮንንና የአቶ አለምነው መኮንን ቡድን፣ “ለህወሃት ተገዢዎች ሆነን መቀጠል የለብንም” የሚለውን ቡድን ለመምታት ከህወሃት ጋር ሆኖ ያሴራው ሴራ ነው በማለት ፣ ህወሃትን የሚቃወሙ ቡድኖች ይገልጻሉ። ባለፈው አንድ ወር ብቻ በርካታ የፖሊስ አዛዦች ስራቸውን ለቀዋል። የተወሰኑትም በኮማንድ ፖስት መሪዎች ታስረዋል። የክልሉ የጸጥታ ሁኔታ ሙሉ በሙሉ የሚቆጣጠረው በህወሃት በሚመራው ኮማንድ ፖስት ነው። በሌላ በኩል የግል የጦር መሳሪያ የታጠቁ ዜጎችን ትጥቅ ለማስፈታት በኮማንድ ፖስቱ የተጀመረው እንቅስቃሴ ሰሞኑን ተጠናክሮ ቀጥሎአል። በተለይ በሰሜን ጎንደር የሚገኙ አርሶአደሮችን ትኩረት ባደረገው በዚህ እንቅስቃሴ፣ አርሶአደሮች መሳሪያቸውን ላለማስረከብ ሲሉ በጫካ እንዲያድሩ እየተገደዱ ነው።

No comments:

Post a Comment