Thursday, November 17, 2016

በኢንተርኔት አፈና ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ቀዳሚ ሆነች ።

ኅዳር ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በዜጎቻቸው ላይ አፈና በማድረግ የመረጃ እቀባ ከሚያደርጉ አገራት ውስጥ ቻይና፣ ሶሪያ እና ኢራንን በመከተል ኢትዮጵያ በዓለም አራተኛ፣ በአፍሪካ ደግሞ በአንደኝኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን ፍሪደም ሃውስ አስታውቋል። በኢንተርኔት ስርጭት ሁዋላ ቀር የሆነችው ኢትዮጵያ በኢንተርኔት ተጠቃሚ ዜጎቿ ላይ በምታደርገው እቀባዎችና አፈናዎች ግን ቀዳሚ ሆናለች ብሎአል።

አንድ ዓመት ያስቆጠረውን የኢትዮጵያን ሕዝባዊ አመጽ ተከትሎ በመላው ኢትዮጵያ የሚታየው የኢንተርኔት ስርጭአፈና ይበልጥ ተጠናክሮ መቀጠሉን ጥናቱ አትቷል። በኦሎምፒክ የማራቶን ሩጫ ውድድር የብር ሜዳሊያ ተሸላሚው አትሌት ሌሊሳ ፈይሳ እጆቹን በማጣመር በኢትዮጵያ ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ለዓለም ሕዝብ እንዲታወቅ ካደረገ ወዲህ፣ የኢትዮጵያ ባላስልጣናት ለስድስት ወራት የሚዘልቅ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በማውጣት የኢንተርኔት አገልግሎቶችን በመዝጋት አፈናውን ይበልጥ አጠናክረውታል። አገዛዙ የሞባይል ኢንተርኔት፣ ፌስቡክ፣ ዋትስ አፕ እና ቫይበርን የመሳሰሉ የኢንተርኔት አገልግሎቶችን ጨምሮ የባህርማዶ መገናኛ ብዙሃንን ሙሉ ለሙሉ ዝግ ማድረጉንም ሪፖርቱ አመልክቷል።
በኢንተርኔት ነጻነት ደቡብ አፍሪካ የተሻለች አገር በመባል በዓለም 25ኛ በአፍሪካ የመጀመሪያውን ስፍራ ስትይዝ፣ ጎረቤት አገር ኬኒያ በበኩሏ በዓለም 29ኛ በአፍሪካ 2ኛ፣ ናይጀሪያ በዓለም 34ኛ በአፍሪካ 3ኛ ደረጃን ይዘዋል። ኢትዮጵያ በዓለም 83 ደረጃን ይዛለች። በኢትዮጵያ ያለው የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ስርጭት 12 በመቶ ብቻ ነው። በኢትዮጵያ የሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት በወር በአማካኝ 85 የአሜሪካ ዶላር ክፍያ ሲጠየቅበት፣ በኬኒያ እና ኡጋንዳ 30 የአሜሪካ ዶላር ይጠየቅበታል። ከአፈናው በተጨማሪ የዋጋ ውድነቱ ከፍተኛ መሆኑንም ጥናቱ አመላክቷል።

No comments:

Post a Comment